በናይጄሪያ ፕሬዚደንት ቢሮ ውስጥ የተከፈተው "ሐሰተኛ ተቋም" ኃላፊ በቁጥጥር ሥር ዋለ
በናይጄሪያው ፕሬዚደንት ቢሮ ውስጥ እንደተቋቋመ የተገለፀው ሐሰተኛ ተቋም ኃላፊ ለሳምንታት ሲፈለግ ከቆየ በኋላ በቁጥጥር ሥር ዋለ።
አዴኒይ አዴይሚ ማቲው የተባለው ግለሰብ 'ፕሬዚደንሻል ፌሪን ኢንቨስትመንት ፕሮሞሽን' በሚል ለመሰረተው ተቋም ዋና ዳይሬክተር እንደሆነ ይገልጻል።
ፕሬዚደንቱ እና ቢሯቸው ግን ስለተቋሙም ሆነ ስለዳይሬክተሩ ሹመት የሚያውቁት ነገር እንደሌለ ተናግረዋል።
ይህንንም ተከትሎ በ950 ሺህ ዶላር በተመሰረተው ሐሰተኛ ተቋም ላይ የሙስና ምርመራ እንዲደረግ አዝዘዋል።
ግለሰቡ መጀመሪያ ላይ ጥፋተኛ አለመሆኑን ለአገሪቷ መገናኛ ብዙኃን የተናገረ ሲሆን የቀረበበትን ሐሰተኛ እና የማስመሰል ክሶች ቀርቦ በመከላከል ስሙን እንደሚያድስ ገልጾ ነበር።
ሆኖም ይህንን ማድረግ ባለመቻሉ የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት የእስር ማዘዣ አውጥቶበታል።
ማቲው ለሳምንታት ተሰውሮ ከቆየ በኋላ በደቡብ ምዕራቧ ኦሱን ግዛት በቁጥጥር ሥር ውሏል።
ጉዳዩ ፕሬዚደን ቦላ ቲኑቡ ባለፈው ሳምንት በማያውቁት ተቋም ላይ የሙስና ምርመራ እንዲደረግ ካዘዙ በኋላ በናይጄሪያ መነጋገሪያ ሆኗል።
የፕሬዚደንቱ ቢሮ፣ የጽሕፈት ቤቱ ኃላፊ ፊርማ ያለበት እና ግለሰቡ ራሱን የሾመበት ደብዳቤ ሐሰተኛ መሆኑን አረጋግጧል።
የፍርድ ቤቱ የክስ መዝገብ እንደሚያስረዳውም አደይሚ እና ሌሎች ሁለት ግለሰቦች ምክር ቤቱን ለማቋቋም ሐሰተኛ ሰነድ በማዘጋጀት፣ በርካታ የባንክ አካውንቶችን በተቋሙ ስም በመክፈት እና መሬት ላይ ለሌለ ተቋም ሕጋዊ እውቅና በመፈለግ ተከስሰዋል።