በኢትዯጵያ በኮቪድ-19 የተያዙ ሰዎች ቁጥር 32,722 ደረሰ

በኢትዮጵያ በኮሮናቫይረስ መያዛቸው በምርመራ የተረጋገጠ ሰወች ቁጥር 32,722 የደረሰ ሲሆን ከእነዚህም መካከል 544 ሕይወታቸው ማለፉን የጤና ሚኒስቴር መግለጫ ያሳያል። እስካሁን ድረስ በቫይረሱ ተይዘው ያገገሙ ሰዎች ቁጥር ደግሞ 12,524 መሆኑን ይኸው የጤና ሚኒስቴር መግለጫ ያትታል። በኢትዮጵያ ቫይረሱ በከፍተኛ ሁኔታ ከተሰራጨባቸው ስፍራዎች መካከል አዲስ አበባ ቀዳሚ ስትሆን እስካሁንም 19,881 ሰዎች በቫይረሱ መያዛቸው ተረጋግጧል። ኢትዮጵያ ከዚህ ቀደም በ24 ሰዓት ውስጥ ምርምራ የምታደርገው 10000 ለሚሆን ናሙና የነበረ ቢሆንም፣ አሁን ግን ከ15 000 በላይ መመርመር ጀምራለች። እስከ ትናንትናው ድረስም በአጠቃላይ የመረመረቻቸው ናሙናዎች ብዛት 629 210 ደርሷል።ሳይዘናጉ አስፈላጊውን ጥንቃቄ በማድረግ ራሳችንንና ሌሎችን ከበሽታው እንጠብቅ።

የቀጥታ ሽፋን

  1. አውስትራሊያ የክትባት ሙከራው ከተሳካ ለዜጎቿ በነፃ ለመስጠት ቃል ገባች

    አውስትራሊያ ተስፋ የጣለችበት የኮሮናቫይረስ ክትባት ከተሳካ ለ25 ሚሊየን ሕዝቦቿ ክትባቱን በነፃ ለመስጠት ቃል ገባች።

    ክትባቱ እየተሰራ ያለው በመድሃኒት አምራቹ ኩባንያው አስትራዜኔካ እና ኦክስፎርድ ዩኒቨርሲቲ ነው። የክትባቱ ሙከራ ከተሳካና ከኩባንያው ጋር ስምምነት ላይ ከተደረሰ በቅድሚያ ለአውስትራሊያዊያን በነፃ እንደሚሰጥ ጠቅላይ ሚኒስትር ስኮት ሞሪሶን ተናግረዋል።

    ኦክስፎርድና አስትራዜኔካ እየሰሩ ያሉት ይህ ክትባት ወደ መጨረሻው ደረጃ ለመድረስ ተስፋ ከተጣለባቸው አምስት ክትባቶች መካከል አንዱ ነው።

    በመሆኑም “ክትባቱ ስኬታማ ከሆነ በቀጥታ በራሳችን ማምረትና ማቅረብ እንጀምራለን፤ ከዚያም ለ25 ሚሊየን አውስትራሊያ ሕዝቦች በነፃ እንሰጣለን” ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትሩ አክለዋል።

    ለሁሉም ሕዝብ ክትባቱ ለማቅረብ ምን ያህል ሊያስወጣ እንደሚችል ያልተወሰነ ቢሆንም አውስትራሊያ ከአሜሪካው የመድሃኒት አምራች ኩባንያ ከቤክቶን ዲኪንሰን ጋር 100 ሚሊየን መርፌዎች አቅርቦት የ25 ሚሊየን ዶላር ስምምነት ተፈራርማለች።

    አውስትራሊያ የክትባት ስምምነት ለመጀመሪያ ጊዜ የተፈራረመችውም ከአስትራዝኔካ ጋር ነው ተብሏል።

    በአውስትራሊያ እስካሁን ከ400 በላይ ሰዎች በቫይረሱ ሳቢያ ሕይወታቸው አልፏል። በዚህ ወር መጀመሪያ ቪክቶሪያ ግዛት በቫይረሱ የሚያዙ ሰዎች ቁጥር በመጨመሩ አስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ያወጀች ሲሆን ጥብቅ የሆነ የእንቅስቃሴ ገደብም ጥላለች።

    በግዛቷ ከ7 ሺህ በላይ ሰዎች በቫይረሱ የተያዙ ሲሆን ይህም በግዛቷ ስጋትን ፈጥሯል።

  2. ባለፉት 24 ሰዓታት 1386 ሰዎች በቫይረሱ መያዛቸው ተነገረ

    ባለፉት 24 ሰዓታት ለ22ሺህ 101 ሰዎች የኮሮናቫይረስ ምርመራ ተደርጎ፤ 1ሺህ 386 ሰዎች በቫይረሱ መያዛቸውን የጤና ሚኒስቴርና የሕብረተሰብ ጤና ተቋም ባወጡት ዕለታዊ መግለጫ አስታውቀዋል።

    ይህም በአገሪቱ በቫይረሱ መያዛቸው የተረጋገጡ ሰዎችን ቁጥር 32ሺህ 722 አድርሶታል።

    ከዚህ በተጨማሪ ባለፉት 24 ሰዓታት 414 ሰዎች ከበሽታው ሲያገግሙ የ28 ሰዎች ሕይወት ማለፉ ተነግሯል።

  3. ፈረንሳይ በሥራ ቦታዎች የአፍና አፍንጫ መሸፈኛ ማድረግን አስገዳጅ ልታደርግ ነው

    ፈረንሳይ በቫይረሱ የሚያዙ አዳዲስ ሰዎች ቁጥር በመጨመሩ በአብዛኛዎቹ የሥራ ቦታዎች የአፍና አፍንጫ መሸፈኛ ማድረግን አስገዳጅ ልታደርግ ነው።

    አዲሱ ሕግ በፋብሪካዎች እና ሰዎች በጋራ በሚጠቀሙባቸው ቢሮዎች ውስጥ ተግባራዊ ይሆናል ተብሏል።

    ውሳኔ ከ12 ቀናት በኋላ ተግባራዊ መሆን ይጀምራል የተባለ ሲሆን፤ በግል ቢሯቸው የሚሰሩ ሰዎችን ግን አይመለከትም።

    እስካሁን የአገሪቷ መንግሥት በሥራ ቦታ የአፍና አፍንጫ መሸፈኛ ማድረግን የሚመክረው አካላዊ ርቀትን መጠበቅ በማይቻልባቸው ሥፍራዎች ነው።

    በአገሪቷ ከሐምሌ ወር ጀምሮ በኮሮናቫይረስ የሚያዙ ሰዎች ቁጥር ጨምሯል።

    በአንድ ቀን በአማካይ በቫይረሱ ሲያዙ የነበሩ ሰዎች ቁጥር ባለፉት ሦስት ሳምንታት በእጥፍ ጨምሮ በቀን የሚያዙ ሰዎች ቁጥር 2 ሺህ ደርሷል።

    በፈረንሳይ 256 ሺህ ሰዎች በቫይረሱ የተያዙ ሲሆን ከ30 ሺህ በላይ ሰዎች ደግሞ ሕይወታቸው አልፏል።

  4. የቻይናው ድርጅት በዓመቱ መጨረሻ የኮቪድ -19 ክትባት ዝግጁ እንደሚሆን አስታወቀ

    የቻይና የመድሃኒት አምራች ድርጅት በተያዘው የፈረንጆቹ ዓመት መጨረሻ የኮቪድ -19 ክትባት ዝግጁ ይሆናል ተብሎ እንደሚጠበቅ አስታወቀ።

    የዚህ ሲኖፋርም የተባለው ድርጅት ኃላፊ ሊዩ ጂንግዠን ለኮቪድ -19 ክትባት ይሆናል ተብሎ የሚጠበቀው አንደኛው ክትባት አሁን ላይ በዩናይትድ አረብ ኤምሬቶች ደረጃ ሦስት በሰዎች ላይ በሚደረግ ክሊኒካል ሙከራ ላይ እንደሚገኝ ለመገናኛ ብዙኃን ተናግረዋል።

    ይህ ክትባት በታህሳስ ወር መጨረሻ ላይ ገበያ ላይ ይውላል ተብሎ ይጠበቃል።

    ኃላፊው ራሳቸውም ሁለት መጠን [ዶዝ] ክትባት እንደወሰዱና እስካሁን ምንም ዓይነት የጎንዮሽ ጉዳት እንዳልገጠማቸው ለግሎባል ታይምስ ተናግረዋል።

    ቻይና በቤጂንግ በዓመት 120 ሚሊየን ዶዝ እና በዉሃን ደግሞ 100 ሚሊየን ዶዝ ማምረት የሚያስችል ማዕከላት አሏት።

    ክትባቱ ለሁለት ዶዝ ከ144 ዶላር ባነሰ ዋጋ ለገበያ ይቀርባል ተብሏል።

    ይሁን እንጂ ዋጋውን አስመልክቶ አንዳንድ ቅሬታዎች ይነሳሉ። የቻይና የማህበራዊ ሚዲያ ተጠቃሚዎች ዋጋው በገጠር ለሚኖሩና የኢኮኖሚ አቅማቸው ዝቅተኛ የሆኑ ሰዎችን አቅም ሊፈታተን ይችላል እያሉ ነው።

    ቻይና አሁን ላይ በአገር ውስጥ በቫይረሱ የተያዘ ሰው አልመዘገበችም። በቫይረሱ የተያዙ ሰዎች ከውጪ የገቡ ናቸው። ነገር ግን በገጠራማ አካባቢ ወረርሽኙ ሊያገረሽ ይችላል የሚል መጠነኛ ስጋት አለ።

    በዓለማችን ከ200 የሚበልጡ ክትባቶች በምርምር ላይ ሲሆኑ ከእነዚህ መካከል ከ20 የሚበልጡት በሰዎች ላይ የክሊኒካል ሙከራ ደረጃ ላይ ደርሰዋል።

  5. የዓለም ጤና ድርጅት ‘የኮቪድ-19 ክትባትን ብሔራዊ ጥቅም’ መሆን እንደሌለበት አስጠነቀቀ

    ከሌሎች ይልቅ የራሳቸውን ፍላጎት በማስቀደም የኮቪድ-19 ክትባት ለመስራት በሚሞክሩ አገራት ወረርሽኙ እየተባባሰ መሆኑን የዓለም ጤና ድርጅት ዳይሬክተር ተናገሩ።

    ይህንን ወረርሽኝ በፍጥነት መቆጣጠር ከፈለግንና ኢኮኖሚውን እንደገና መጀመር ካለብን ለበሽታው ተጋላጭ የሆኑ በየትኛውም አገር ላይ ያሉ ሰዎች ላይ ትኩረት ማድረግ ያስፈልጋል ብለዋል።

    ዶ/ር ቴዎድሮስ "አገራት የራሳቸውን ሕዝብ ብቻ ለመጠበቅ የሚያደርጉት ጥረት ብቻ ወረርሽኙን ለመቆጣጠር አያስችልም፤ ለዚህ ወረርሽኝ የምንሰጠው ምላሽ በጋራ መሆን አለበት" በማለት አሳስበዋል።

    ምንም እንኳን ክትባት ማግኘት የእያንዳንዱ አገር ብሔራዊ ፍላጎት ቢሆንም “ሁሉም ሰው ደህንነቱ እስካልተጠበቀ ድረስ ማንም ደህና አይሆንም” ብለዋል ዶ/ር ቴዎድሮስ አድሃኖም።

    በመሆኑም ዳይሬክተሩ 'የኮቪድ-19 ክትባትን ብሔራዊ ጥቅም' ከማድረግ ልንከላከል ይገባል ብለዋል።

    ዳይሬክተሩ አክለውም በርካቶች ለክትባቱ መገኘት በሚደረገው ጥረት እንዲሳተፉ የሚጠይቅ ደብዳቤ ለሁሉም የድርጅቱ አባላት መላካቸውን አስታውቀዋል።

  6. የቫይረሱ መነሻ የነበረችው ዉሃን ወደ ቀደመ ድምቀቷ ተመለሰች

    በቻይናዋ ዉሃን በሺዎች የሚቆጠሩ ሰዎች ትከሻ ለትከሻ ተደጋግፈው፣ የአፍና አፍንጫ መሸፈኛ ሳያደርጉ በውሃ ላይ መንሳፈፊያዎች ላይ ሆነው በሙዚቃ ድግስ ሲዝናኑ ታይተዋል።

    ይህ ምስል በዚህ ዓመት የተነሳ ነው ብሎ ማንም ከባድ ለሆን ይችላል። ይሁን እንጂ ይህ የሆነው ባሳለፍነው ቅዳሜ እና እሁድ የኮሮናቫይረስ መነሻ እንደሆነች በምትታመነው ዉሃን ከተማ ነው።

    በውሃን ማያ ባህር ዳርቻ የውሃ ፓርክ የታየው ትዕይንትም ሌላው ዓለም በበሽታው ፍዳውን እያየ እርሷ ግን ሙሉ ለሙሉ ከበሽታው የተላቀቀች አስመስሎታል።

    ይህም በርካቶችን አነጋግሯል። በውሃን ከግንቦት ወር አጋማሽ ጀምሮ በሕብረተሰቡ ውስጥ በኮሮናቫይረስ የተያዘ ሰው አልተመዘገበም።

    ባለሙያዎች ግን አሁንም በከተማዋ በቫይረሱ የተያዘ ሰው ባይኖርም፤ ከውጭ ሊገባ ይችላል፤ በመሆኑም በርካታ ቁጥር ያላቸው ሰዎች አንድ ላይ መሰባሰባቸው አደገኛ ነው ሲሉ እያስጠነቀቁ ነው።

  7. ናይጄሪያ ዓለምአቀፍ በረራ ልትጀምር ነው

    ናይጄሪያ ከ11 ቀናት በኋላ አየር መንገዷን ለዓለም አቀፍ ተጓዦች ክፍት እንደምታደርግ የአገሪቷ መንግሥት አስታወቀ።

    የአቪየሽን ሚኒስተር ሃዲ ሲሪካ በትዊተር ገፃቸው ባሰፈሩት ፅሁፍ የአገሪቷን ዋና መዲና አቡጃንና የንግድ ማዕከሏ ሌጎስ አየር ማረፊያዎች ስራ እንደሚጀምሩ ገልፀዋል።

    ሌሎች ሂደቶችና ፕሮቶኮሎች ዝርዝር በቀጣይ እንደሚገለፅ ሚኒስትሩ አክለዋል።

    በኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ ሳቢያ የናይጄሪያ አየርማረፊያዎች ለዓለም አቀፍ የመንገደኞች በረራ ዝግ የተደረጉት መጋቢት ወር ላይ ነበር።

    በአገሪቷ የአገር ውስጥ በረራ ባለፈው ሳምንት የተጀመረ ሲሆን ዓለም አቀፍ በረራ መጀመሩም የአፍሪካ ትልቁን ኢኮኖሚ ቀስ በቀስ የማንቀሳቀስ አካል ነው ተብሏል።

    በናይጄሪያ እስካሁን ከ49 ሺህ በላይ ሰዎች በቫይረሱ የተያዙ ሲሆን የ975 ሰዎች ሕይወት አልፏል። 36 ሺህ የሚሆኑት ደግሞ ከበሽታው ማገገማቸው ተገልጿል።

  8. በኢትዮጵያ ተጨማሪ 1460 ሰዎች በቫይረሱ ሲያዙ የ16 ሰዎች ሕይወት አለፈ

    በኢትዮጵያ ባለፉት 24 ሰዓታት በተደረገ 19 ሺህ 747 ናሙና ምርመራ 1 ሺህ 460 ሰዎች በቫይረሱ መያዛቸው መረጋገጡን የጤና ሚኒስቴርና የሕብረተሰብ ጤና ተቋም ባወጡት መግለጫ አስታውቀዋል።

    በዛሬው ዕለትም በቫይረሱ የ16 ሰዎች ሕይወት ያለፈ ሲሆን ይህም አጠቃላይ የሟቾቹን ቁጥር 544 አድርሶታል።

    በሌላ በኩል ባለፉት 24 ሰዓታት 165 ሰዎች ከበሽታው ያገገሙ ሲሆን በአጠቃላይ 12 ሺህ 524 ሰዎች አገግመዋል።

    አጠቃላይ በቫይረሱ የተያዙ ሰዎች ቁጥርም 31 ሺህ 336 ደርሷል።

    የቫይረሱ ሥርጭት እየጨመረ ሲሆን ሥርጭቱን ለመግታት "ምክንያት አልሆንም" የሚል የአፍና አፍንጫ መሸፈኛ ማድረግ ላይ ግንዛቤ ለመፍጠር የተለያዩ ዘመቻዎች እየተደረጉ ነው።

    መጭውን የቡሄ በዓልም ልጆች በቤታቸው ሆነው እንዲያከብሩ ጤና ሚኒስቴር አሳስቧል።

  9. የስፔን አራት ግዛቶች አዳዲስ ገደቦችን ጣሉ

    የስፔን አራት ተጨማሪ ግዛቶች የቫይረሱ ሥርጭት በመጨመሩ አዳዲስ ገደቦችን አስተዋወቁ።

    ግዛቶቹ አንዳሉሲያ ፣ ጋሊሲያ፣ ካንታብሪያ እና ካስቲሌና ሌኦን ናቸው።

    የተጣሉት ገደቦች የምሽት መዝናኛ ቤቶች እንዲዘጉ፣ ምግብ ቤቶችና ባሮች ከእኩለ ሌሊት በኋላ አገልግሎት እንዳይሰጡ እንዲሁም ሌሊት ሰባት ሰዓት ላይ እንዲዘጉ የሚሉትን ያካትተታል።

    አካላዊ ርቀትን መጠበቅ ካልተቻለ ከቤት ውጭ ሕዝብ በሚገለገልባቸው ቦታዎች ማጨስም ተከልክሏል።

    በሌላ በኩል ሰሜናዊ ባስኪዩ ግዛት አስቸኳይ የጤና አዋጅ ታውጃለች ተብሎ ይጠበቃል። ይህም ከጎረቤት ግዛቶች በተሻለ ጥብቅ ገደቦችን ለመጣል ያስችላል ተብሏል።

    ስፔን ለሦስት ወራት ጥላው የነበረውንየእንቅስቃሴ ገደብሰኔ መጨረሻ ላይ ካነሳች በኋላ በቫይረሱ የሚያዙ ሰዎች ቁጥር እየጨመረ ነው። በቫይረሱ ሳቢያ የሞቱ ሰዎች ቁጥርም ከ28 ሺህ 600 በላይ ሆኗል።

  10. ዩናይትድ ኪንግደም በርካታ በጎ ፈቃደኞችን ለኮቪድ-19 ክትባት ምርምር እየመዘገበች ነው

    የዩናይትድ ኪንግደም ብሔራዊ የጤና አገልግሎት በኮሮናቫይረስ ላይ ለሚያደርገው ምርምር ከ100,000 በላይ በጎ ፈቃደኞችን ቢመዘግብም አሁንም ተጨማሪ ያስፈልጉኛል እያለ ነው።

    ደህንነቱ የተጠበቀ እና ውጤታማ ክትባት ለማግኘት እጅግ በርካታ ሰው በበጎ ፈቃደኝነት እንዲሳተፍ ይፈለጋል ተብሏል።

    ተመራማሪዎቹ ከፍተኛ ቁጥር ያላቸውን በጎ ፈቃደኞች የሚፈልጉት ደግሞ አነስተኛ ቁጥር ካላቸው ዜጎች፣ እድሜያቸው ከ65 በላይ የሆኑ አዛውንቶች በአጠቃላይ “ ከፍተኛ ትኩረት የሚሰጣቸው ቡድኖች” መካከል ነው።

    የዩኬን ክትባት ግብረ ኃይል የምትመራው ኬት ቢንግሃም እንዳለችው “ እነዚህ ሙከራዎች ደህንነታቸው የተጠበቀ ነው. . . በክሊኒክ የሚደረገውን ሙከራ በፍጥነት አውጥተን መፈተሽ በቻልን ቁጥር በፍጥነት ክትባቱን ማግኘት እንችላለን” ብላለች።

    እስከ መጪው ታህሳስ ወር ድረስ የኦክስፎርድ ዩኒቨርስቲ የሰራውና ከፍ ላለ ሙከራ የበቃው ክትባትን ጨምሮ ከአስር የማይበልጡ የኮቪድ-19 ክትባቶች በክሊኒክ ውስጥ ሙከራ ይደረግባቸዋል ተብሏል።

  11. ሩዋንዳ የቫይረሱ ሥርጭት በመጨመሩ የገበያ ቦታዎችን ዘጋች

    የሩዋንዳ ዋና መዲና ኪጋሊ ባለሥልጣናት የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ ሥርጭት መጨመሩን ተከትሎ ሁለት ትላልቅ ገበያዎችን ለሰባት ቀናት ያህል እንዲዘጉ ውሳኔ አስተላለፉ።

    ውሳኔው ከዛሬ ጀምሮ ተግባረዊ እንደሚሆን ተገልጿል።

    ኒያሩጌንጌ እና ክዋሙታንጋ የተባሉት እነዚህ የገበያ ቦታዎቹ በከተማዋ ምግቦች በጅምላ የሚሸጥባቸው ናቸው።

    የገበያ ቦታዎቹ እንዲዘጉ የሚያዘው ውሳኔ በትናንትናው ዕለት የተላለፈ ሲሆን፤ የጤና ሚኒስተር በአገሪቷ 101 አዲስ ሰዎች በቫይረሱ መያዛቸውንና ከእነዚህ መካከል 80ዎቹ በዋና መዲናዋ ኪጋሊ የተገኙ መሆናቸውን ካስታወቀ በኋላ ነው።

    አገሪቷ ባለፉት ሦስት ቀናት ብቻ 253 አዲስ በቫይረሱ የተያዙ ሰዎችን የመዘገበች ሲሆን አብዛኞቹ የተገኙት በኪጋሊ ነው። ቀደም ብሎ በ14 ቀናት ውስጥ የተመዘገበው በቫይረሱ የተያዙ ሰዎች ቁጥር 222 ነበር።

    እንደ አገሪቷ ጤና ሚኒስቴር መረጃ ሩዋንዳ እስካሁን 2 ሺህ 453 በቫይረሱ የተያዙ ሰዎችን የመዘገበች ሲሆን፤ ከ300 ሺህ በላይ ናሙናዎችን መርምራለች። ከቫይረሱ ጋር በተያያዘም የስምንት ሰዎች ሕይወት አልፏል።

    ሩዋንዳ ነዋሪዎቿ ወደ አውሮፓ አገራት እንዲገቡ የተፈቀደላት ከሰሃራ በታች ያለች ብቸኛው አገር ናት።

  12. ከፍንዳታው በኋላ በቤይሩት የእንቅስቃሴ ገደብ እንዲጣል ጥሪ ቀረበ

    የሌባኖስ የጤና ሚንስቴርን በባላደራነት እያስተዳደሩ የሚገኙት ሃማድ ሃሰን ከፍንዳታው በኋላ የቫይረሱ ስርጭት በመጨመሩ በቤይሩት የእንቅስቃሴ ገደብ እንዲጣል ጥሪ አቀረቡ።

    ሃማድ ሃሰን የእንቅስቃሴ ገደቡ ለሁለት ሳምንታት እንዲዘልቅ ጠይቀዋል።

    በሌባኖስ ባለፉት 24 ሰዓታት በቫይረሱ የተያዙ ሰዎች ቁጥር 439 መሆኑን እና 6 ሰዎች ደግሞ ከቫይረሱ ጋር በተያያዘ ህይወታቸው ማለፉን የአገሪቱ ጤና ሚኒስቴር አስታውቋል።

    የተባበሩት መንግሥት ድርጅት በበኩሉ በሌባኖስ በሚገኙ የስደተኞች መጠለያ ካምፕ ውስጥ 4 ሰዎች በቫይረሱ ምክንያት ህይወታቸው ማለፉን ያረጋገጠ ሲሆን፤ "በሌባኖስ ነገሮች ከቁጥጥር ውጪ ሊሆኑ ይችላል" ሲል አስጠንቅቋል።

  13. ደቡብ አፍሪካ ዳግም አልኮል እና ሲጋራ እንዲሸጥ ፈቀደች

    ደቡብ አፍሪካ ተጥለው የቆዩትን የኮሮናቫይረስ ክልከላዎች ማላላት ጀምራለች። ዛሬ ደግሞ የአልኮል እና ሲጋራ ሽያጭን ፈቅዳለች።

    ፕሬዝደንት ሲሪል ራማፎሳ፤ የአገር ውስጥ ጉዞዎችን እና ቤተሰብ አንድ ላይ እንዲሰበሰብ የፈቀዱ ሲሆን፤ የንግድ ተቋማትም ከዛሬ ጀምሮ ደንበኞቻቸውን ማስተናገድ ይችላሉ ብለዋል።

    ከዚህ ቀደም ፕሬዝደንቱ የአልኮል መጠጥ የጤና ስርዓቱ ላይ ጫና እያሳደረ ነው በማለት የአልኮል ሽያጭን ከልክለው ነበር።

    ደቡብ አፍሪካ ከ570ሺህ በላይ ሰዎች በቫይረሱ የተያዙባት ሲሆን ከ11ሺህ 500 በላይ ሰዎች ደግሞ ህይወታቸውን አጥተዋል።

  14. ባለስልጣናት ለቫይረሱ ስርጭት የቤተክርስቲያን መሪን ተጠያቂ አደረጉ

    የደቡብ ኮሪያ ባለስልጣናት በአገሪቱ በቅርቡ ላገረሸው የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ ሳራንግ ጄል የተባለ ቤተ-ክርስቲያን መሪን ተጠያቂ አደረጉ።

    ባለስልጣናቱ የዚህ ቤተ-ክርስቲያን መሪ የኮሮናቫይረስ ክልከላዎችን ተላልፈው ጸረ-መንግሥት የሆነ የተቃውሞ ሰልፍ ጠርተዋል ብለዋል።

    ጁን ክዋንግ-ሁን የተሰኙት ግለሰብ የቤተ-ክርስቲያኗ አባላት ዝርዝርን አሳልፌ አልሰጥም በማለታቸው ለአባላቱ የኮሮናቫይረስ ምርመራ እንዳይደረግ እክል ፈጥረዋልም ተብሏል።

    ባለስልጣናቱ እስከ 3400 ሊሆኑ የሚችሉ የቤተ-ክርስቲያኒቷ አባላት እራሳቸውን ወደ ለይቶ ማቆያ እንዲያስገቡ ጠይቀዋል።

    ደቡብ ኮሪያ ቫይረሱ እንደ አዲስ ሲያገረሽ መነሻውን በማጥናት ለመቆጣጠር ጥረት ስታደርግ ቆይታለች።

  15. በሕንድ በኮሮናቫይረስ የሞቱ ሰዎች ቁጥር ከ50ሺህ አለፈ

    በሕንድ ከኮሮናቫይረስ ጋር በተያያዘ ህይወታቸው ያለፈ ሰዎች ቁጥር ከ50ሺህ ተሻገረ።

    ይህን ያለው የሕንድ የጤና ሚንስቴር ነው።

    ሕንድ ከአሜሪካ፣ ብራዚል እና ሜክሲኮ በመቀጠል በርካታ ሞት የተመዘገበባት አራተኛዋ አገር ሆና ተቀምጣለች።

    እስካሁን በሕንድ 2.6 ሚሊዮን ሰዎች በቫይረሱ መያዛቸው የተረጋገጠ ሲሆን፤ የአገሪቱ ባለስልጣናት ሰዎች በቫይረሱ የሚያዙበት የፍጥነት መጠን እየቀነሰ ነው ብለዋል።

    የሕንድ ጠቅላይ ሚንስትር ናሬንድራ ሞዲ፤ የቫይረሱን ስርጭት ለመቆጣጠር ከሚወሰዱት ተግባራት መካከል በቀን ለ1 ሚሊዮን ሰዎች ምርመራ ማድረግ አንዱ እና ዋነኛው መሆኑን መናገራቸው ይታወሳል።

  16. ከ1.5 ሚሊየን በላይ ናይጄሪያውያን ተማሪዎች አገር አቀፍ ፈተና ሊወስዱ ነው

    ከ1.5 ሚሊየን በላይ የሚሆኑ ናይጄሪያውያን የሁለተኛ ደረጃ ተማሪዎች ከዛሬ ጀምሮ አገር አቀፍ ፈተናቸውን መውሰድ እንደሚጀምሩ ተገለጸ።

    ተማሪዎቹ ላለፉት ሁለት ሳምንታት ፈተናውን ለመውሰድ ዝግጅት ሲያደርጉ ነበር። ከኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ ጋር ተያይዞ ደግሞ ከመጋቢት እስከ ሐምሌ ወር ድረስ ሊሸፍኑት የሚገባው ትምህርት ተቋርጦ ነበር።

    የትምህርት ቤቶች ኃላፊዎች ፈተናውን ተማሪዎች በሚወስዱበት ወቅት የቫይረሱን ስርጭት ለመግታት አካላዊ ርቀታቸውን ጠብቀው እንደሚቀመጡ ገልጸዋል።

    ተማሪዎቹ ፈተናውን የሚወስዱት በሚቀጥለው ዓመት ከፍተኛ ትምህርት ተቋማትን ለመቀላቀል ነው።

    ናይጄሪያ በ19 ሺ ትምህርት ቤቶች የሚማሩና ከፍተኛ የትምህርት ተቋማትን ለመቀለቀል በዝግጅት ላይ ያሉ ከ1.5 ሚሊየን በላይ ተማሪዎች አሏት።

  17. ጃፓን በታሪኳ አይታው የማታውቀው የኢኮኖሚ ድቀት አጋጠማት

    ግዙፍ ከሚባሉት ኢኮኖሚዎች ተርታ የምትመደበው ጃፓን ከኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ ጋር በተያያዘ ከባድ ፈተና ውስጥ መግባቷ ተገልጿል።

    በዓለማችን ሶስተኛው ትልቁ ኢኮኖሚ የያዘቸው ጃፓን ከሚያዝያ እስከ ሰኔ ባሉት ወራት ውስጥ ብቻ አጠቃላይ የአገር ውስጥ ምርቷ 7.8 በመቶ ቀንሷል።

    ጃፓን ከኮሮረናቫይረስ ወረርሽኝ በፊትም ቢሆን ኢኮኖሚዋ በፍጥነት ማደግ ተስኖት ነበር።

    ዛሬ በወጡ መረጃዎች መሰረት በዓለም ኢኮኖሚዎች ላይ የደረሰው ዱብዳ በጃፓንም ላይ እየተየ መሆኑን አመላክቷል።

    በዚህም መሰረት አገሪቱ በታሪኳ አይታው የማታውቀው የምጣኔ ሃብት ድቀት አጋጥሟታል።

  18. በመቶዎች የሚቆጠሩ ጭምብል የማድረግ ግዴታን ተቃውመው አደባባይ ወጡ

    በስፔን መዲና ማድሪድ በመቶዎች የሚቆጠሩ ሰዎች የአፍ እና አፍንጫ መሸፈኛ ጭምብል ማድረግ ግዴታ መሆን የለበትም በማለት የተቃውሞ ሰልፍ አካሄዱ።

    ተቃዋሚዎቹ የኮሮናቫይረስ ስርጭትን ለመቆጣጠር የተጣሉ ሌሎች ገደቦችንም ተቃውመዋል።

    የአፍ እና አፍንጫ መሸፈኛ ጭምብል ማድረግ ግዴታ የነበረው የህዝብ ትራንስፖርት ለሚጠቀሙ ሰዎች ብቻ ነበር፤ ይህ አስገዳጅ ሕግ ግን ለሁሉም ዜጋ እንዲጸና ሆኗል። ከዚህ በተጨማሪም ህዝብ በሚሰበስብበት ቦታ ሲጋራ ማጨስ ተከልክሏል።

    ስፔን ከአውሮፓ አገራት መካከል በኮሮናቫይረስ ክፉኛ የተጠቃች አገር ናት። አሁንም ዳግም የቫይረሱ ስርጭት እያየለባት ይገኛል።

    እስካሁን በአገሪቱ በቫይረሱ ሳቢያ ህይወታቸው ያለፈ ሰዎች ቁጥር ከ28ሺህ በላይ ሆኗል።

  19. ኒው ዚላንድ በኮሮናቫይረስ ስጋት ምርጫ አራዘመች

    የኒው ዚላንድ ጠቅላይ ሚንስትር ጃሲንዳ አርደርን በኮሮናቫይረስ ስርጭት ስጋት አጠቃላይ ምርጫውን በአንድ ወር አራዘሙ።

    የኒው ዚላንድ አጠቃላይ ምርጫ መስከረም 9 እንዲካሄድ ታቅዶ የነበረ ቢሆንም በአንድ ወር ተራዝሞ ጥቅምት 7 እንዲደረግ ተወስኗል ሲሉ ጠቅላይ ሚንስትሯ አስታውቀዋል።

    በዚህ ሳምንት መጀመሪያ ላይ የቫይረሱ ስርጭት የጨመረባት ትልቋ የኒው ዚላንድ ከተማ ኦክላንድ፤ የእንቅስቃሴ ገደቦች ተጥሎባታል።

    ጠቅላይ ሚንስትሯ ከአንድ ሳምንት በላይ ምርጫውን የማራዘም ፍላጎት እንደሌላቸውም ተናግረዋል።

    ተቃዋሚዎች ግን ምርጫው ከአንድ ወር በላይ እንዲገፋ ፍላጎት አላቸው። የጠቅላይ ሚንስትሯ ተቀናቃኝ የሆነው ብሔራዊ ፓርቲ፤ የእንቅስቃሴ ገደብ ተጥለው ባለበት ወቅት ምርጫ ወይም የምርጫ ቅስቀሳ የሚካሄድ ከሆነ ለገዢው ፓርቲ መልካም አጋጣሚ ነው በማለት ይከራከራሉ።

    ለሶስት ወራት ያክል በቫይረሱ የተያዘ ሰው ያልተገኘባት ኒው ዚላንድ በቅርቡ በቫይረሱ የተያዙ በርካታ ሰዎችን መዝግባለች።

    በኦክላንድ ብቻ 58 በቫይረሱ የተያዙ ሰዎች ተገኝተዋል።

  20. እንዴት አደራችሁ?

    ውድ የቢቢሲ አማርኛ ቤተሰቦች እንደምን አደራችሁ?

    የቀጥታ ዘገባ ገጻችን ተጀምሯል።

    ከኮሮናቫይረስ ስርጭት ጋር የተያያዙ ከአገር ውስጥ እና ከውጪ የተገኙ ትኩስ መረጃዎችን እናደርሳችኋለን።

    አብራችሁን ቆዩ።

    መልካም ቀን።